Monday, April 30, 2012

ቅዱስ ጊዮርጊስ

       በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር የዓመቱ ፪፻፴፫ኛው ዕለት ነው። ከዚህ ዕለት በኋላ እስከ ዓመቱ መጨረሻ ድረስ፣ በዘመነ ዮሐንስ ፻፴፫ ዕለታት ሲቀሩ፤ በዘመነ ማቴዎስ፤ ማርቆስ እና ሉቃስ ደግሞ ፻፴፪ ዕለታት ይቀራሉ።
       የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይሄንን ዕለት ሰማዕቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ የሞተበትን ዕለት ማስታወሻ አድርጋ ትዘክረዋለች፡
        “በዘአዕረፈ እግዚእየ ማር ጊዮርጊስ ገብሩ ለኢየሱስ ክርስቶስ በዘተከለለ ወርኁ በጽርዕ ጵንፍልዮ ስሙ ዘበትርጓሜሁ ሚያዝያ አመ ፳ወ፫ ለሠርቅ ወዕለቱሂ ዓርብ በጊዜ ፱ቱ ሰዓት አሜን።”
                “የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አገልጋይ ጌታዬ ቅዱስ ጊዮርጊስ ያረፈበት ሰማዕትነቱን የፈጸመበት ወሩ በጽርዕ ጵንፍልዮ ይባላል። ይኸውም ሚያዝያ ነው ወሩ በባተ በሃያ ሦስት ቀን ዕለቱም ዓርብ በዘጠኝ ሰዓት ነው አሜን።”

Friday, April 27, 2012

የጎንደር ደብረ ኀይል ወደብረ ጥበባት በዓታ ለማርያም የአቋቋም ምስክር ትምህርት ቤት ግንባታ ውል ተፈረመ፡፡


ሚያዝያ 18/2004 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ
Gedamate 3ማኅበረ ቅዱሳን በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት የሚገኘውን የደብረ ኀይል ወደብረ ጥበባት በዓታ ለማርያም የአቋቋም ምስክር ትምህርት ቤትን በ4.6 ሚሊዮን ብር ለመገንባት ሚያዚያ 12 ቀን 2004 ዓ.ም. የግንባታ ውል ስምምነት ከአስማማው አያሌው ሕንጻ ሥራ ተቋራጭ ጋር ተፈራረመ፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የማኅበራዊ ልማት ዋና ክፍል አስተባባሪነት የሚከናወነው ይኸው ፕሮጀክት ማኅበረ ቅዱሳንን በመወከል የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ ዲ/ን ሙሉጌታ ኀ/ማርያምና የሕንፃ ሥራ ተቋራጩ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ አስማማው አያሌው አማካይነት የፊርማ መርሐ ግብሩ ተፈጽሟል፡፡

Thursday, April 5, 2012

ከክህነት ስለሚያስሽሩ ምክንያቶች አንዳንድ ነጥቦች ከፍትሐ ነገሥት


(ደጀ ሰላም፤ መጋቢት 27/2004 ዓ.ም፤ ኤፕሪል 5/2012)በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዋሺንግተን ዲሲና አካባቢው ሀ/ስብከት አዲስ ሊቀ ጳጳስ ተሹሞ ተልኳል ከተባለበት ከጥቅምት ወር 2004 ዓ.ም ጀምሮ በችግር ላይ ይገኛል። ሊቀ ጳጳሱ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በሀ/ስብከቱ ውስጥ ያሉ አብያተ ክርስቲያናት በቃለ ዓዋዲው መሠረት የመረጡትን ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አልቀበልም ከማለት አልፈው ካህናቱን በሙሉ ማስፈራራት እና አንዳንዶቹንም "አውግዣለሁ" ማለት ጀምረዋል። ይህም መነሻ ሆኖን "ካህናትን ከክህነታቸው ስለሚያስሽሩ ምክንያቶች"፣ በደፈናው ከመሬት ተነሥተው "ክህነት ይዣለሁ" ስለሚሉ አቡነ ፋኑኤልን ስለመሳሰሉ ጳጳሳት አስቀድመው በቅዱሳን አበው የተሠራውን ሕግ በተመለከተ ፍትሐ ነገሥቱ የሚለውን ከዚህ እንደሚከተለው እናቀርባለን።
+++

ከ175 በላይ በገና ደርዳሪዎች ሊመረቁ ነው


በማኅበረ ቅዱሳን ልማት ተቋማት አስተዳደር የአቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል ከ175 በላይ በገና ደርዳሪዎችን መጋቢት 29 ቀን 2004 ዓ.ም. እንደሚያስመርቅ አስታወቀ፡፡
የትምህርትና ሥልጠና ማእከሉ ሓላፊ አቶ አብዮት እሸቱ እንደገለጹት ማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ በፊት በዜማ ማሠልጠኛ ክፍሉ በርካታ በገና ደርዳሪዎችን ማስመረቁን ገልጸው የአሁኖቹን ተመራቂ ጨምሮ ከ1200 በላይ በገና ደርዳሪዎቹን በማእከሉ ማሠልጠኑን ገልጸዋል፡፡

መጋቢት 29 ቀን 2004 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ከቀኑ 7፡30 በሚካሔደው የምረቃ መርሐ ግብር ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የተመራቂ ቤተሰቦችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንደሚገኙ የገለጹት የማእከሉ ሓላፊ ማኅበረ ቅዱሳን ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጠው መተዳደሪያ ደንብ መሠረት የቤተ ክርስቲያንን እምነት፣ ሥርዐት፣ ትውፊትና ዶግማ ተጠብቆ ወደ ቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ የተሰጠውን ሓላፊነት እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የአቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል በአሁኑ ወቅት ከ KG እስከ 9ኛ ክፍል ተማሪዎችን በቀለም ትምህርት እያስተማረ የሚገኝ ሲሆን በዜማና በአብነት የትምህርት መስክ ሥልጠናዎችን እየሰጠ እንደሚገኝ አቶ አብዮት ገልጸዋል፡፡